2014 ማርች 2, እሑድ

ደግሞ ምርጫ መጣ?!

ለነገሩ የምርጫ ሰሞን ፖለቲከኞቻችን እነሆ መነቃቃት እንዲይዛቸው በርካቶች እየታተሩላቸው ነው፡፡ ቀስቃሽ የሚሹ ፖለቲከኞቻችን ዛሬም ሌላ መነቃቂያ እና የሚያነቃ ይፈልጋሉ መሰለኝ፡፡
እሹሩሩ የሚላቸው፡፡ ወፌ ቆመች የሚላቸው የሚሹ ይመስላሉ፡፡ ይህ ታዲያ ለመቼውም ቢሆን የሚጠቅም አልመሰለኝም፡፡ ስለሆነም ልላቸው ወደድኩ፡፡ ሁላችሁም ብትሆኑ የት ገባችሁ?
እኔ በደንብ ስለማውቀውና በኢትዮጵያ ታላቅ ነው ብዬ የማስበውን የዴሞክራሲያዊ ክዋኔ (ተዓምር) ሁሌም እናፍቀዋለሁ፡፡ በተለይም በወቅቱ እኔ የዩኒቨርሲቲ ተማሪ የነበርኩ በመሆኑ፡፡ 1997 ዓ.ም. ለእኔ ልዩ ነበር፡፡ የነጻነት አመት ይመስለኛል፡፡ በፖለቲካ ትርክት ውስጥ ኢትዮጵያ ታላቅ ነገር አየች ከተባለ ለእኔ ከዋነኞቹ ታሪካዊ ትርክቶች መካከል የወቅቱ የምርጫ ሂደት አንዱ ነበር ለማለት እወዳለሁ፡፡ እኔ በነበርኩበት ዩኒቨርሲቲም ታዲያ የነበረው ድባብ ዛሬም ድረስ ትውስ ይለኛል፡፡ እውነት ለመናገር ክርክራችን ልዩ ነበር፡፡ ለሁሉም ወንድሞቻችን ክብር አለኝ፡፡
በዩኒቨርሲቲው ውስጥ የነበሩ ከተለያዩ ብሔሮችን ብሔረሰቦች የተውጣጡ ተማሪዎች በፖለቲካ አመለካከታቸው ልዩነት ላይ ተንተርሰው ያሳዩ የነበሩት ነገር ዛሬም ድረስ ትርጉም አለው ለእኔ፡፡ በተለይ በጊዜው በርካታ ነገሮች ሲከወኑ እንመለከት ነበርና ግ-ር-ም ይለኛል፡፡ በተለይ ደግሞ በተለያዩ የወቅቱ ፓርቲዎች መሪዎች የሚሰጡትን መግለጫ እያሳደዱ ማዳመጥ ትንታኔ መስጠትና መከራከር ልዩ መለያችን ነበር፡፡ በግቢው ውስጥ በፖለቲካ ልዩነት ይነሱ የነበሩ አንዳንድ አላስፈላጊ ነገሮች የነበሩ ቢሆንም፤ ሁሉም ለአመለካከቱ ይከፍል የነበረው ዋጋ ልዩ ነበር በእነዚህ ጊዜያት ታዲያ በወቅቱ የነበሩት ወንድሞቼና እህቶቼ ትዝ ይሉኛል፡፡ በተለይ እንዲህ ምርጫ አጀንዳ ለመሆን በሚዳዳባቸው ጊዜያት ሁሉ ትውስ ይለኛል፡፡
የአመለካከት ልዩነታችን እንዳለ ሆኖ፤ ደጋግ ወንድሞቻችን እንደነበሩ ሁሉ አሳልፎ መሥጠት የሚወዱ አንዳንድ ተማሪ ወንድሞቻችን እንደነበሩም አስታውሳለሁ፡፡ ነገር ግን ሁሉም አለፈ፡፡ ይህ ሁሉ በሆነ ግዜ ታዲያ በርካታ ሁነቶች ታልፈው ለዛሬ በቅተናል፡፡ በወቅቱ በነበሩ ግርግሮች መነሻነት እስር ቤት ተገብቶ የተገባበት፤ ጥቁር መልበስም የተከለከለበት ጊዜ ሁሉ ነበር፡፡ የፓርቲ መሪዎች ምግብ አልበላንም ባሉን ግዜ ጮኸናል፡፡ ከለሊቱ ዘጠኝ ሰዓት ድረስ ብርድ ላይ እንድንቀመጥ ተፈርዶብን በብርድ ተቀጥተናል፡፡ ምናልባት ምርጡ ጊዜ ነው፡፡ በወቅቱ ያሳለፍናቸውን ሁነቶች ዛሬ ላይ ሆኖ ማሰብ ደስ የሚል ነገር ይፈጥራል፡፡ ግና ሁሉም አለፈ ዛሬ፡፡
ለማንኛውም በቀጣይ ሁነቶቹንና ሌሎችንም አንስተን እንጨዋወታለን፡፡ ግን ደግሞ ምርጫን አስመልከቶ ከተቀለዱ ቀልዶች መካከል አንዱ ትውስ አለኝ፡፡ የሰማውን የነገረኝ አንድ ወዳጄ ነው፡፡  
በቀደመው ግዜ ከነበሩት ምርጫዎች በአንዱ ሆነ ያሉትን እያነሳ ይነግረኛል፡፡ በመሠረቱ ምርጫው እየተካሄደ ነው፡፡ ከዚያም አንደኛው መራጭ መርጦ ይወጣል፡፡ ምርጫውን አጠናቆ ካበቃ ወዲያ ወደጉዳዩ ለማቅናት መንገድ ሲጀምር ሌላ ወዳጁን ያገኝና ማንን እንደመረጠ በጠየቀው ግዜ ሰውየው ተቃዋሚዎችን መምሩጡን ይነግረዋል፡፡ ሆኖም፤ ሰውየው ለምን ኢህአዴግን አልመረጥክም ብሎ ይሞግተዋል፡፡ ከብዙ ክርክር ወዲያ እርሱም በቃ እንግዲህ ምን ላድርግ አንድ ግዜ መርጫለሁ፤ አሁን ምን ማድረግ አለብኝ ኢህአዴግን ለመምረጥ ብሎ ይጠይቃል፡፡ ወዳጁ መለሰለት፡፡ ለምን ሄደህ ምርጫ ታዛቢዎችን አታማክራቸውም ብሎ፡፡ ወዲያውም ሄደ፡፡ ከዚያም ለታዛቢዎቹ የሆነውን አስረዳቸው፡፡ ምርጫውን ማስተካከል እንደሚፈልግ፡፡ ነገር ግን እንዴት ማድረግ እንዳለበት እንዳላወቀ፡፡ ምን እናድርግ ታዲያ ብለው ጠየቁት አሉ፡፡ ሰውየውም ለማስተካከል አንድ እድል ስጡኝ ማለት፡፡ ይሄኔ አንደኛው ታዛቢ ፈጠን ብሎ ይመልሳል፡፡ ለማንኛውም ለሌላ ግዜ እንዳትሳሳት፡፡ ለዛሬው ቀድመን አስተካክለንልሃል፡፡
ምርጫችንን አውቆ ቀድሞ ከስህተታችን የሚያስተካክለን ይስጠን ብለን ብንጸልይስ? ጸሎታችንን ሰምቶ አምላክ ቢሰጠንስ? እውነት ለዚህ የተዘጋጀ ፓርቲ ይኖር ይሆን?

ሠላም ሁኑ!

አብርሃም ተስፋዬ

ምንም አስተያየቶች የሉም:

አስተያየት ይለጥፉ