2014 ኤፕሪል 13, እሑድ

የደብተራው አምሳሉ ጡዘት!!!

http://www.goolgule.com/my-reply/ ሠዓሊ (ደብተራ) አምሳሉ ገ/ኪዳን ለቀደመው ጽሁፉ አስተያየቶች የሠጠውን ምላሽ በመንተራስ የተጻፈ፡፡

ለምላሽህ ምላሽ ቢሆን

ደብተራው አምሳሉ የቅድመ አያቶቹን ታሪክ ይዞ ፉከራና ቀረርቶውን ያስነካዋል፡፡ ነጻነትህ ጥሩ ሆኖ ሳለ፤ ደብተራነትህ ሳይጎዳህ የቀረ አልመሰለኝም፡፡ ግድ የለህም ጎድቶሃል፡፡ ምላሽ ይሁናችሁ ብለህ የደገምከው የመሰል አያቶችህን ተረት ነው፡፡ የዛን ዘመን ተረት ደግሞ ታሪክ እንዲሆን ትወዳለህ፡፡ በሌላ ወገን ያለውን ለማመን ግን አሻፈረኝ ባይነትህ ገርሞኛል፡፡ በመሠረቱ የወደዱትን ጽፈው ታሪክ አስብለው ያለፉት ያንተው ነገስታት እነሆ ዛሬ ላይ ታሪክ አልባ ሀገር ብትኖረን ተጠያቂ እንደሚሆኑ አስባለሁ፡፡ የእራሳቸውን ማንነት ለማግዘፍ ሲሉ፤ ቅራቅንቦዋቸውን ሁሉ በመዝገብ ሲያኖሩ ከርመው፤ አንዳች እውነት ፍለጋ ምን ያህል እያደከሙን እንዳሉ ሳስብ አዝናለሁ፡፡ ነገስታቱ በረባ ባልረባው ሁሉ የእነርሱን ጀብድና መልካምነት አስፍረው አልፈዋል፡፡ አንዳንዴም ሳስበው በንግስናቸው ወራት ጦርነት ባልነበረበት ሁሉ ጀብድ ያስመዘገቡ ይመስለኛል፡፡ ገራሚ ናቸው ብቻ፡፡ እነርሱን በመሀከሉም ማንሳቴ ስለማይቀር ወዳንተ ልመለስ፡፡

በ‹‹እነሆ ምላሻችሁ›› ጽሁፍህ ለማንሳት የሞከርካቸው ሀሳቦች በዋናነት ለአንድ ግለሰብ ጽሁፍ ላይ የተንተራሰ ቢሆንም፤ ለሁላችሁም መልስ ይሆናል በማለትህ አንብቤዋለሁ፡፡ ነገር ግን አሁንም ሊገባኝ አልቻለም፡፡ ሀሳብህ የኦሮሞን ህዝብ ኢትየጵያዊነት ለመጠራጠርህ በድጋሚ ከማረጋገጥ የዘለለ አልሆንልህ ቢለኝ ደጋግሜ አነበብኩት፡፡ ሀሳብህን በእርግጠኝነት ስሜት ስታነሳ ጥንቃቄ የሚጎድልህ መሰለኝ፡፡ አንብበህ ያወቅከውን ነገር ከነማስረጃው ብትናገረው መልካም የሚሆን ይመስለኛል፡፡ ሲወርድ ሲዋረድ የመጣ ነው ካልክም በዛው መልክ ብናውቀው ጥሩ ነበር፡፡ አንተ ግን ከወቅቱ ‹‹ታሪክ›› ጸሐፍት አንዱን ወክለህ አልያም ሆነህ የምትጽፍ ይመስላልና ምናልባት ደግመህ ብታየው፡፡ ሆኖም ታዲያ የቃላት ድርድር በዛበትና አሰለቸ፡፡ አንዱን ሳትጨርስ ወደአንዱ ትዘላለህ፡፡ መልክ አሳጣኸውና ግራ ለማጋባት ያደረግከውም መሰለኝ፡፡ ስለምን አንተ ያልከው ሁሉ ተቀባይነት እንዳለው እንዳሰብክም አላውቅም፡፡ እራስህን ግን ምን ይህል እንደምትወድ አስታውቆብሃል፡፡

ለዘመናት ከኦሮሞነት ጋር በተያያዘ ለሚነሱ ማናቸውም የታሪክ ክርክሮች ማሳያ ተደርገው የሚነሱትን ‹‹አለቃ›› የሚል ቅጥያ የተሰጣቸው አድርባዮች የጻፉትን ይዘን እስከመቼ እንደምንዘልቅ አላውቅም፡፡ እነርሱ ላንተና ለመሰሎችህ እንዲመች አድርገው ባሰናዱት አይነት ሳይሆን፤ ሌሎች ምሁራን ደግሞ ጉዳዩን መርምረው ያሰፈሩትንም ማጣቀስ ተገቢ ይመስለኛል፡፡

በመሰረቱ፤ ዋናው አጀንዳ የነበረው የአኖሌ የመታሰቢያ ሐውልት ይመስለኛል፡፡ ይህ ደግሞ በእርግጥም ሰማዕታትን ለማሰብ የሆነ ስለሆነ መልካም ነው ብሎ ማለፍ ክፉ አያስብልም፡፡ ያንን ዕልቂት በቅጡ የሚያስታውሱት፤ ህመሙ የሚሰማቸው፤ ቁስሉ እስካሁን የሚኮሰኩሳቸው እኒያ የዛው አካባቢ ተወላጆችና፤ በዚሁ ዳፋ እልቂት ያስተናገዱት የአርሲ ልጆች፣ እናቶች፣ አዛውንቶችና መላው ማህበረሰቡ ነው፡፡ ስለሆነም ይሁነኝ ልጆቼን፣ ወንድሞቼን፣ እናቶቼን፣ አባቶችን፣ በአጠቃላይም ወገኖቼን ላስብ ያለው የአርሲ ብሎም የኦሮሞ ህዝብ ወገኖቹን ለማሰብ ለምን ይከለከላል? በመሠረቱስ አፍን ሞልቶ ተረት ነው ለማለት መድፈር ህዝብን ‹‹ታሪክህን አታውቅም›› ከማለት በምን ያለይ ይሆን?

የኦሮሞ ጥናት ማህበር እ.ኤ.አ. በ1995 ባሳተመው የጥናት መድብል ሁለተኛው ቅጽ ላይ አባስ ሀጂ (ዶ/ር) የአርሲ ኦሮሞ ህዝብ አጼ ምኒልክ ላይ ያሳየውን ፖለቲካዊና ወታደራዊ ጥንካሬ አስመልከቶ ባሰፈረው ጥናታዊ ጽሑፍ ላይ ‹‹የአርሲ ህዝብ ለምን እና እንዴት ያን ያህል ብዛት ያለው ተዋጊ ኃይል ለረዥም አመታት በማንቀሳቀስ፤ ኢጣልያን በወቅቱ በአንድ ጦርነት ለመርታት የቻለውን ምኒልክን ለመuuም ተቻለው?›› የሚለው ጥያቄ ማንም ሊጠይቀው የሚችለው እንደሆነ ይጠቅሳል፡፡
በወቅቱም የአርሲ ኦሮሞ እራሱን ለመከላከል የወሰዳቸውን እርምጃዎች ያትታል፡፡ የምኒልክን አቅም በቅጡ የተፈተነበትም እንደነበር ያሳያል ይኸው ከላይ የተነሳው ጥያቄ፡፡ ከዚሁ ጋር ተያይዞም ታዲያ አርሲዎችን ጠቅሞዋቸው ነበር ያላቸውን ምክንያቶች ዘርዝሮዋል፤ ከእነርሱ ውስጥም የሚከተሉት ይገኙበታል፡፡

የቦታውን አቀማመጥና አርሲዎች በዚህ ያገኙትን ጠቀሜታ በአንደኝነት እንደምክንያት ያነሳዋል፡፡ አንዳንድ ጊዜ ተፈጥሮም ታዳላለች የሚባለው አይነት ሊሆን ይችላል፡፡ ከዚሁ ጋር ተያይዞ ታዲያ ምንም እን£ በርካቶች የአርሲ ህዝብ በወቅቱ በአዋሽና ሸበሌ ወንዞች መሐል ብቻ የሚኖር አድርገው ቢገምቱም፤ ከዛም ባሻገር አርሲ ከኦሮሞ ብሔር ውስጥ አንዱና ትልቁ ‹‹ቅርንጫፍ›› መሆኑን የዘነጉት ይመስላል፡፡ በዚህም መነሻነት የህዝቡ ቁጥር ከፍተኛ የነበረ መሆኑም አግዞታል ማለት ነው ይለናል ዶ/ር አባስ፡፡

የውስጥ ሰላምና አንድነቱ ለአርሲ ሌላኛው ጥንካሬው ነበር፡፡ ወራሪውንም በብርቱ የሞገተው ለዛም ነው፡፡ እንደጎረቤቱ ቦረና የውስጥ ሽኩቻ አልነበረበትም፡፡ በአንድ ወቅት እንደውም በተለይም ከቀደምቶቹ መካከል የሆኑት ቃቃ ኦሮሞ በሰጡት ትዕዛዝ መሠረት ኦሮሞ ኦሮሞን እንደማይገድልና አርሲም ለዚሁ ትዕዛዝ ተገዢ እንደነበር ያነሳል ዶ/ሩ፡፡ ሆኖም፤ እንደሌሎቹ የኦሮሞ ታሪኮች ሁሉ ይህም ታሪክ በጊዜ ሂደት እንዲጠፋ ሆነ፡፡

ተያይዞም፤ አርሲ ምንም እን£ በጎሳ የተለያየ ቢሆንም ለወራሪና ሌላ ባዕድ ሊነካው ሲሞክር በአንድነት ሆኖ ይመክት እንደነበርና ለዚሂም ያሳይ የነበረውን መነሳሳት ነው ጥናቱ የሚያወሳው፡፡
በአርሲ ወገን ሆነው ህዝቡን ሲያስተባብሩና አመራር ሲሰጡ ከነበሩት መካከል በጥናቱ ሶስቱ ተጠቅሰዋል፡፡ እነርሱም፤ ሱፋ ቁሶ፣ ሌንጂሶ ዲጋ እና ሮባ ቡታ ናቸው፡፡ እኒህ ጀግኖች ታዲያ በአልደፈርም ባይነት ለህዝብ ጥቅም የተዋደቁ ናቸው፡፡ በእነርሱ መሪነት በሺዎች የሚቆጠር የአርሲ ኦሮሞ ላለመወረር ሲል ህይወቱን ሰጠ፡፡ እኒህ ግለሰቦች ጥሩ የጦር መሪዎች፤ ፖለቲከኞችና ህዝብን መምራት የሚችሉና የቻሉ ነበሩ በወቅቱ፡፡ የአርሲን ብርታት ያየው ምኒልክ ታዲያ ያለርህራሄ ሁሉንም ባሻውና ይጠቅመኛል ባለው መልክ አደረገ፡፡ ጭፍጨፋው ዘግናኝ እንደነበር መዛግብት ያወሳሉ፡፡ አንተ እንደምትለው አይደለም፤  ደብተራ አምሳሉ፡፡ ነገሩ ብርቱ ነው፡፡
በአንድ አጋጣሚም ስለመገንጠል አንስትሃል፡፡ የኦሮሞ ህዝብ ትግልና ጥያቄ ሲነሳ ለምን ከመገንጠል ጋር ብቻ ተያይዞ እንደሚነሳ አላውቅም፡፡ ይህም ስህተት ነው፡፡ ለአሁን እንተወውና በሌላ ጊዜ ካልሆነ እመለስበታለሁ፡፡

ለማንኛውም፤ጸሐፍት ተብለው የሚነሱትን ሰዎች አስመልክቶ ነጋድራስ ገ/ህይወት ባይከዳኝ፤ ከዚህ በፊት በሌሎች ጽሁፎቼም እንዳነሳሁት በወቅቱ (ያን ጊዜ ማለት ነው) የነበሩትን ጸሐፍት ለሁለት ከፍሎ ማየት እንደሚገባ በአንድ መጽሐፋቸው ላይ ጥሩ አድርገው ገልጸውታል፡፡ ሲያብራሩም የመጀመሪያዎቹን ሊቃውንት ቤተመንግስት ሲላ;ቸው፤ እንጀራን ሲፈልጉ ከቤተመንግስት ተጠግተው በንጉሱ የታዘዙትንና ንጉሱን የሚያወድሱ ነገሮችን ታሪክ ብለው በመጻፍ ለላው ትውልድ የሚያስቆዩ ሲሆኑ ሌሎቹ ደግሞ መነኮሳት መሆናቸውን ይጠቅሳሉ፡፡ መነኮሳቱ የሚጽó<ቸው ታሪኮች አድልዎ ይበዛበታል ሲሉ ያስረዳሉ፡፡ እራሳቸውን ለማዋደድ ሲሉ የወቅቱ ‹‹ተዓማኒነታቸውን›› ተጠቅመው ታሪክ ብለው የእራሳቸውን የውስጥ ጥላሸት ታሪክ ብለው አስፍረውታል፡፡ የራሳቸውን እንጂ የህዝቡን ጥቅምና ጉዳት ከቶ አይቆጥሩምና፡፡ ስለዚህ የልባቸውን የሚፈጽምላቸው ንጉስ ቅዱስ ይሉታል፡፡ ከድንቁርናቸው ወጥቶ ከፍ ባለ ህሊና ተመርቶ ስለዜጎቹ ልማት የሚጥር ግር እርኩስ፡፡ አንተስ ደብተራ አምሳሉ እንዴት ትላቸው ይሆን?

ሌላውና በጣም ገራሚው ነገር ደግሞ የሐይማኖት መዛግብቱም ውስጥ ጉዳዩ እንዲካተት መሆኑ ነው፡፡ ይህንን በማድረግ ሀይማኖቱንም ሌላ መልክ ለማስያዝ ይጥራሉ፡፡ በጣም የሚገርመው ታዲያ ስለጉዳዩ አቶ አጽመ ጊዮርጊስ የተባሉት ግለሰብ በአንድ ወቅት ያሰፈሩት ከዚህ እንደሚከተለው ነው፡፡ ‹‹በዳግማዊ ምኒልክ ዘመን ጋላ ሁሉ ተገዛ፤ ባማራ ሕግና ሥርዓት ሄደ፤ ካህናቱ ግን አንድ ጋላ አስተምረው አላጠመቁም፡፡ ይልቅስ ተፊተኛው ቂም የበለጠ ቂም በልቡ አኑረውበት መሬቱን በቀላድ ወሰዱበት፡፡ አንድ ቀላድ የቅስና አንድ ቀላድ የአወዳሽ እያሉ በዚሁ ስብከት ንጉሱን አሳመኑ፡፡ ስለመንግስት ያሰቡ መስለው ለንጉሱም አንድ ቀላድ፣ ለገባር አንድ ቀላድ፣ ለወታደር አንድ ቀላድ....መሬቱን ተካፍለው ጋላን አንደባርያ አድርገው ይገዙታል እንጂ የክርስቶስን መንገድ አላሳዩትም፡፡ እነሱም አልተማሩም፡፡ አስተማሪው ቢመጣ ይከለክላሉ፡፡ ከትልቁ ሁሉ ከንቱ ብላሽ የሚያደርገው በቁጥርም እርሱም እግዚአብሔርን አለማወቃቸው ነው፡፡ ማለት ሕጉንና ትእዛዙን በሁሉም ስፍራ መኖሩን አያውቁም፡፡››

አየህ አይደል ደብተራ አምሳሉ? ይህም የአንተና የእኔ የኢትዮጵያ ታሪክ ነው ተብሎ ይጻፋል፡፡ እነዚህንም እናነባለን፡፡ አንተ ላንተ የሚመች የመሰለህን መሰል ነገር ታሪክ ነው ብለህ ልትሞግተኝ ትሞክራለህ፤ ብለህ ደግሞ ታሪክ ከእኔ ወዲያ ለማለትም ትዳዳለህ፤ እኔ ግን ልልህ ወድጃለሁ፤ በመሀከል ያለችው ግን ኢትዮጵያ ናት፡፡ ይህች ኢትዮጵያ ደግሞ እውነቱን አፍረጥርጠን ለጠፋውም ለለማውም የሆነውን ሁሉ ተነጋግረን አውቀን፤ እውነተኛውን ነገር እስካልያዝን ድረስ ዝም ብለን ተነስተን፤ የምንደነፋባት መሆን የለባትም፡፡

የተመቸንን በሰማን ቁጥር ‹‹እውነቱ ይሄ ነው›› ብለን በምንለው ልክ፤ እውነቱን ስንሰማ ታወቀብኝ በሚል ስሜት ከምንንደረደር፤ ሀገራዊውን የቆሸሸ ታሪክ አምኖ ተቀብሎ ወደፊት ስለማይኖረን ወይም እንዳይኖረን ከምንመርጠው መጥፎ ታሪክ ላይ ብንሰራ መልካም ነው፡፡ ‹‹ከእዛ ዘመን ደብተራ የዚህ ዘመን ደብተራ›› ብለን እንድንናገር አድረገን፡፡



አብርሃም ተስፋዬ